25/06/2026
ከፍተኛ የማህበረሰብ ጤና ስጋት እየሆነ የመጣውን ህገ ወጥና ጥራቱን ያልጠበቀ የመድሃኒት ዝውውር ችግር ለመቅረፍ ውጤታማና ተመጋጋቢ የቁጥጥር ስርኣት መዘርጋት እንደሚገባ ተጠቆመ ።
ሰኔ 18/2018 ለአለም ማህበረሰብ ከፍተኛ የጤና ስጋት እየሆነ የመጣውን ህገ ወጥና ጥራቱን ያልጠበቀ መድሃኒት ዝውውርና የአጠቃቀም ጉድለት ችግር ለመቅረፍ ውጤታማና ተመጋጋቢ የቁጥጥር ስርኣት መዘርጋት እንደሚገባ ተጠቁሟል።
የኢትዮጵያ ምግብና መድሃኒት ባለስልጣን እና በክልሉ ጤና ቢሮ የጤናና ጤና ነክ ተቋማትና ግብኣቶች ቁጥጥር ባለስልጣን በጋራ ባዘጋጁት መድረክ ላይ እንደተጠቆመው ችግሩን ለመቅረፍ የማህበረሰብ ግንዛቤን ከማሳደግ ባለፈ በጠንካራ እርምጃዎች የታጀበ የቁጥጥር ስርኣት መዘርጋት ይገባል።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ሃላፊ አቶ ሳሙኤል ዳርጌ እንደገለጹት ከጦር መሳሪያ በላይ ከፍተኛ ስጋት እየሆነ የመጣው የህገ ወጥ መድሃኒት ዝውውር ፣ የአጠቃቀም ጉድለትና የመጠቀሚያ ጊዜን አለመጠበቅ ችግር ከፍተኛ ትኩረትን ይሻል።
ከዚህ አኳያ የዘርፉ ተቋማት በችግሩ ዙሪያ ህዝብን ከማስገንዘብ ባለፈ ጠንካራ የቁጥጥርና ክትትል ስርኣት ዘርግተው በቁርጠኝነት መንቀሳቀስ ይኖርባቸዋል ብለዋል ።
የኢትዮጵያ የምግብና መድሃኒት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሄራን ገርባ በበኩላቸው የችግሩ አሳሳቢነት እየሰፋ መምጣቱን ገለጸው የሚወሰዱ እርምጃዎች ጠንካራ መሆን እንዳለባቸው ጠቁመዋል ።
ለዚህም የተቆጣጣሪ አካላት ሚና ከፍተኛ እንደሆነ ተናግረዋል ። በተለይ የመድሃኒት አያያዝ፣አጠቃቀምና አወጋገድ ላይ ሰፊ ስራ እንደሚጠብቃቸው አስታውቀዋል ።
ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ተቋማት በሀገሪቱ የወጡ ዝቅተኛ ስታንዳርዶችን አሟልተው ተገቢውን አገልግሎት እንዲሰጡ የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝም ገልጸዋል ።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የጤናና ጤና ነክ ተቋማትና ግብኣቶች ቁጥጥር ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ፋሲካ አለሙ ችግሩን ለመቅረፍ የግሉ ዘርፍና የመንግስት የጤና መዋቅሮች ቅንጅት ወሳኝ ነው ብለዋል።
ይህ ብቻ ሳይሆን አገልግሎት አቅራቢው ፣ ተቆጣጣሪ ውና አገልግሎት ተቀባዩ ማህበረሰብ በችግሩ ስፋትና አሳሳቢነት ዙሪያ የጋራ መግባባት ፈጥረው በተደራጀ መንገድ መንቀሳቀስ ይጠበቅባቸዋል ሲሉም አክለዋል።
እንደ መዋቅር የተቀመጠውን ስታንዳርድ በአግባቡ በማሟላትና ውጤታማና ተመጋጋቢ የቁጥጥር ስርኣት በመዘርጋት ብሎም የዲጅታል መረጃ ስርኣትን በማጎልበት በኩል ሰፊ ስራ እንደሚጠይቅ ተናግረዋል ።
በዳውድ አብደላ