08/03/2026
#አንኮበር
ኢትዮጵያ ሀገሬ ሀገረ እግዚአብሔር ፣
የማርያም አስራት የነገስታት ሀገር ፣
ታሪክሽ ቢወሳ ዝናሽም ቢነገር፣
አያልቅም ተጠቅሶ በሰው ልጅ ከናፍር።
አባይን በጭልፍ ቢሆንም ታሪክሽ፣
ከብዙ አካላትሽ ከብዙ ታሪክሽ፣
የነገስታቱን ምድር አንኮበርን ላንሳልሽ።
በአብርሃ እና አፅብሃ የተመሰረተች ፣
በአፄ ይኩኖአምላክ የተመሰረተች፣
የነገስታት ቦታ የታሪክ ጮራ ነች ።
እነ መርድ አዝማች እነ አምሀኢየሱስ፣
አፅማቸው ያረፈው አንኮበር ጊዮርጊስ ፣
ሣህለ ሥላሴ ኢትዮጵያን የገዛው ፣
አንኮበር ሚካኤልን በክብር የሳነፀው፣
የወለሉን አፈር ከእስራኤል ያስመጣው፣
አፅመም በዚያው ቦታ በክብር የሚገኘው ፣
ያየጥቁር ንጉሥ እምዬ ምኒልክ ፣
የጥቁር ነፃነት የስልጣኔ ልክ፣
ጎንደር ውስጥ ያደገው የኢትዮጵያው መሪ ፣
ስሙ እንኳን ሲጠራ የሚያሰኘው እሪ፣
ያሰው ምኒልክ ነው አንኮበር መስክሪ ።
ምን ብዬ ልግለፃት እምዬ አንኮበርን፣
ለአንቺማ ፈጣሪ አላዳላም ይሆን?
እውነት አምላክ ለአንቺ አላደላም ይሆን ?
እንቁ መስህቦችን በብብትሽ የያዝሽ፣
ጥቂቱን ልመስክር ጥቂቱን ላንሳልሽ።
አንኮበር ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን፣
ሣህለ ሥላሴ ያሳነፀውን፣
ገብስ እህል ከሰማይ ያወረደውን፣
ምሰሶው እስከ አሁን ደዌ ፈዋሹን፣
ሀዋርያዊ መስቀል ምስል የጻድቃን፣
ታሪክ የታየበት ጷግሜ ሶስት ቀን።
እጅግ ያስደንቃል አንኮበር ውበትሽ፣
ብርኩሚት ማርያምን በብብትሽ ይዘሽ፣
ተዓምርሽ ብዙ ነው ብርኩሚት ማርያም፣
ከጎንሽ አለና መዳኛ ለአለም፣
በእቅፍሽ አለና መድሀኔ አለም።
አስቲት ላይ ያለችው ኪዳነ ምህረት፣
በክብር የሞላት ሰባት መቶ አመት።
ቸነፈር ሲበዛ ረሀብ ሲከሰት፣
በአምሀ ኢየሱስ ዘመነ መንግስት፣
ስንዴ ከሰማይ ላይ የወረደባት፣
የመስጫ ማርያምን ምን ብዬ ልርሳት።
የዋሻው ገብርኤል ጎርጎ የሚገኘው፣
በአምሀ ኢየሱስ የተቦረቦረው።
ህዝቅኤል የሰራው ቦታው የሰላም፣
ሚጣቅ ተክለ ሀይማኖት አንድነት ገዳም፣
የአበዉ ቅዱሳን የጠበል መገኛ፣
እውራንን አብሪ የድውይ መዳኛ።
የመነኩሴ ዋሻ እመ ምህረት ያለው፣
መናኝ ጸሎተኛን አቅፎ የሚይዘው፣
ስንቱን ልዘርዝረው ታሪክሽ ብዙ ነወ።
እነ ሊቅ ማረፊያ መሀል ወንዝ ያለው፣
የተማሩ ሰዎች መቀመጫቸው፣
እምዬ ምኒልክ የመሰረተው፣
ሀኪሙ ዶክተሩ ጂኦግራፈሩ፣
ዋና መቀመጫው እዚያ ነው ሰፈሩ።
የጋጀሎ ቦታ ያ የመሀል ወንዙ፣
የባሩድ ማንጠሪያ ጥይት ለአፈሙዙ።
እምዬ አልዬ አምባ የጉምሩክ ከተማ፣
አማራን ከአርጎባ በአንድ የምታስማማ፣
ደምቃ የምትታይ በታሪኳ ማማ።
የአልዬ መኖሪያ ነጋዴው ሲራራ፣
ጥንታዊ መስጊዱ ከሩቅ የሚያበራ።
ወፍ ዋሻ ጥቅጥቁ የተፈጥሮው ደን፣
በእቅፉ የያዘው እንቁ ሶረኔን።
በኢትዮጵያ ታሪክ ትልቅ ቦታ ያለሽ፣
እጅግ ያስደንቃል አንኮበር ውበትሽ።
በዙሪያሽ የያዝሽ እንቁ መስህቦችን፣
እውነት አምላክ ለአንቺ አላደላም ይሆን?
የታሪክ ባለቤት የነገሥታት ምድር፣
ሰዓታት አይበቁም ታሪክሽ ቢነገር፣
ከኢትዮጵያ እንብርት ከሸዋዎች መንደር፣
አንኮበር አንኮበር አንኮበር አንኮበር ።
ገጣሚ፦ ዜና ሸዋበረ (ዜሾ)
ቀን፦ 27/05/2014 ዓ.ም አንኮበር; ኢትዮጵያ