04/03/2026
ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ በአያቶላህ አሊ ኻሜኒ ሞት ሀዘናቸዉን እንደገለጹ ተደርጎ የተሰራጨው ስክሪን ቅጂ ሀሰተኛ ነው ሲል ኢትዮጵያ ቼክ አጋርቷል።
ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ በኢራኑ መንፈሳዊ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ ሞት ሀዘናቸዉን እንደገለጹ የሚያሳይ ስክሪን ቅጂ (screenshot) በተለያዩ በማህበራዊ ትስስር ገጾች እየተጋራ ይገኛል።
ይህ ስክሪን ቅጂ “በወንድሜ አያቶላህ አሊ ኻሚኒ ሞት የተሰማኝን ጥልቅ ሀዘን እገልጻለሁ። ኻሚኒ ላለፉት 40 አመታት ኢራንን በለዉጥ ጎዳና የመሩ ብርቱ ሰው ናቸዉ” የሚል መልዕክት ይዟል። በተጨማሪም “ለቤተሰቦቻቸው፣ ለወዳጅ ዘመዶቻቸው እንዲሁም ለመላ ኢራናዊያን መጽናናትን እመኛለሁ” ይላል።
ኢትዮጵያ ቼክ በብዙዎች ጥቆማ መሰረት የዚህን ስክሪን ቅጂ ትክክለኛነት ለማጣራት በመጀመርያ መልዕክቱ የጠ/ሚሩ የማህበራዊ ሚድያ ገፆች ላይ እንዳለ ቅኝት አድርጎ እንደዚህ አይነት መልዕክት እንደሌለ ተመልክቻለሁ ብሏል።
በሁለተኛነት ይዘታቸው የተቀየሩ ፎቶዎችን ለመመርመር የሚረዳውን ‘Fotoforensics’ ድረ-ገጽን መጠቀሙን ኢትዮጵያ ቼክ ገልጿል።
ይህ ድረ-ገጽ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የፌስቡክ ስም የሚገኝበት የስክሪን ቅጂዉ ክፍል የተነካካ ወይም በኮፒ ፔስት (Copy and Paste) ይዘቱ የተቀየረ እንደሆነ አሳይቷልም ብሏል።
በሌላ በኩል በስክሪን ቅጂዉ ላይ የሚገኘው ይዘቱ የተለጠፈበትን ጊዜ የሚያሳይ መግለጫ (Time Stamp) የፊደላት ቅርጽ (Font) ስህተት እንዲሁም ከበስተቀኙ የሚገኘው የግላዊነት ቅንብር የአለም ምስል (Public Privacy Setting Globe Icon) ደግሞ የአቀማመጥ ግድፈት (Misalignment) ያለበት መሆኑንም መመልከቱን ኢትዮጵያ ቼክ ገልጿል።
በተጨማሪም የስክሪን ቅጂዉ ዋና ይዘት ጽሁፍም በተመሳሳይ መልኩ የተለያዩ ግድፈቶች ያሉበት ሲሆን ይህም በቅንብር የተሰራ እንደሆነ የሚጠቁም ነው ብሏል።
በመጨረሻም፣ መረጃው በተለጠፈ በ14 ደቂቃ ውስጥ 44,500 ግዜ ሪአክሽን እንዳገኘ ማሳየቱ በጠ/ሚሩ የፌስቡክ ገፅ ላይ ያለውን መስተጋብር እንደማያሳይ አይተናል ሲል ኢትዮጵያ ቼክ ጨምሮ ገልጿል።
በሌላ በኩል ግን ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ ኢራን በኩዌት ላይ የፈጸመችውን ጥቃት ተከትሎ ከኩዌት ልዑል አልጋ ወራሽ ጋር በስልክ መወያየታቸው እንዲሁም በአገሪቱ ላይ የሚፈጸም ጥቃትን በጽኑ ማውገዛቸውን የኩዌት የዜና ወኪል መዘገቡም ተገልጿል።
ምንጭ- ኢትዮጵያ ቼክ