24/05/2026
የሀገር መከላከያ ሰራዊት “ጽምዶ“ በሚባለው እንቅስቃሴ በኩል “በኢትዮጵያ ሉዓላዊነት ላይ የሚቃጣ“ ስጋት ቢኖር ስለሚወስደው እርምጃ ለዲፕሎማቲኩ ማኅበረሰብ ማሳወቁን ገለጸ
የመከላከያ የውጭ ግንኙነትና ወታደራዊ ትብብር ዳይሬክተር ሜ/ጄነራል ተሾመ ገመቹ ፤ ይህንን እንቅስቃሴ “ ‘ወደ መሬት እናወርዳለን’ ብለው ስንዝር እንቅስቃሴ” የሚያደርጉ አካላትን አስጠንቅቀዋል።
ሲጀምርም እንቅስቃሴው ፀረ-ሉዓላዊነት መሆኑ የገለጹት ሜ/ጄነራል ተሾመ “ ጫንቃቸውን ለፈርኦን ቀንበር በሰጡ የኢትዮጵያ አካላት እና አካባቢው ላይ ባሉት ስብስብ የተፈጠረ ነው “ ብለዋል።
መከላከያ ሠራዊት ተቀማጭነታቸውን በኢትዮጵያ ያደረጉ የአታሼ ማኅበረሰብ አባላት ስለዚህ ጉዳይ በደንብ እንዲያውቁ እና ግንዛቤ እንዲኖራቸው ሥራ ማከናወኑን አመልክተዋል።
ይህን ማድረግ ያስፈልገው “ ነገ እንደው እቺን ሐሳብ ‘ወደ መሬት እናውርድ’ ብሎ የሚሠራ አካል ካለ የሚሰጠው ምላሽ ለዲፕሎማሲው ማኅበረሰብ አስቀድሞም የተነገረ ጉዳይ “ እንዲሆን በመታሰቡ መሆኑን አስረድተዋል።
“ ከዚህ ሐሳብ (ጽምዶ) ጋር የሚያያዝ ጉዳይ ነገ ትልቅ እርምጃ የሚያስወስድ ጉዳይ ቢነሳ የማንንም ፈቃድ መጠየቅ እንኳ ባያስፈልግ፤ ወዳጆቻችን፣ አብረውን የሚሠሩ ሰዎች የውጪ ሰዎች ይሄን ሐሳብ እንዲገነዘቡ ማድረግ ተገቢ ስለሆነ ነው “ ሲሉ አክለዋል።
ይህ እንቅስቃሴ “ለኢትዮጵያ ሰላምና ደኅንነት አስጊ” ተደርጎ እንደማይወሰድ የተናገሩ ሲሆን ሐሳቡን ለመተግበር የሚደረግ እርምጃን በተመለከተ ግን አስጠንቅቀዋል።
“ እቺኛዋ የጽምዶ ሐሳብ በተመለከተ ፤ ይቺን ቅዠት ‘ወደ መሬት እናወርዳታለን’ ብለው ስንዝር እንቅስቃሴ ቢያደርጉ፣ እንደ ሉዓላዊ አገር ይሄ ተቋም ደግሞ በመንግሥት ግዳጅ እንደተሰጠው ፣ ኃላፊነት እንደተሰጠው፣ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ ሥራ እንደሚሠራ አካል፤ ሰም በእሳት እንደሚቀልጥ ይቀልጣሉ ብለን ነው የምናስበው፣ የምናምነው “ ብለዋል።
በቅርቡ የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች ከሱዳን እና ኤርትራ እንደሆኑ የተገለጹ ግለሰቦች ጋር በፖርት ሱዳን ከተማ ስብሰባ አካሂደው እንደነበርና ዝግጅቱም ከኤርትራ መንግሥት ጋር ግንኙነት ባለው ‘ህድሞና ቲቪ’ የተባለ የዩቲዩብ ቻናል መተላለፉን ቢቢሲ ዘግቧል።