20/08/2023
ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ታሳቢ ተደርጎ የሚዘጋጀው የሀላባ ቁሊቶ ከተማ የክረምት ወራት ውድድር በደማቅ መልኩ እንደቀጠለ ይገኛል።
ነሀሴ 14/12/2015
ዳጉ ስፖርት
==========
በሀላባ ቁሊቶ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ጽ/ቤት አማካኝነት ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ብሎም በከፍተኛ ሊጉ ለሚሳተፈው ሀላባ ከነማ መጋቢ የሚሆኑ ተጫዋቾችን ለማፍራት ታሳቢ ተደርጎ የሚዘጋጀው የክረምት ወራት ውድድር በደማቅ መልኩ መካሄዱን ቀጥሏል።
በዘንድሮ አመት በከተማ አስተዳደሩ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት''ሚሻላ ካፕ''በሚል የተዘጋጀው የአዋቂዎች በትላንትናው እለት ውድድር የጀመረ ሲሆን በመክፈቻው ጨዋታ ቀትር 09:00 ሰዓት ላይ ዞባ ከተጋባዡ ክለብ ከበሸኖ ጋር ተጫውቶ ዞባዎች 2 ለ 1 በሆነ ውጤት ማሸነፍ ችለዋል።
በዛሬው እለትም ሚሻላ ካፕ የቀጠለ ሲሆን ዛሬ ከሰዓት በኃላ ሁለት ጨዋታዎች ተካሂደዋል።
በ8:00 ሰዓት ላይ የሀላባው ሸገርን ከጄ ስፖርት ጋር ያገናኝው ጨዋታ የሀላባው ሸገር 7 ለ 2 በሆነ ሰፊ ጎል ተጋጣሚውን ማሸነፍ ችሏል።
10:00 ሰዓት ላይ ሁለተኛው ጨዋታቸውን ያደረጉት የአቶቲ ኡሎው ጉባ ከተጋባዥ ክለቡ የሾኔው አቻ ጋ ተጫውተው ሁለት አቻ በሆነ ውጤት ነጥብ ተጋርተው ወጥተዋል።
በዕለቱ በተደረጉ በጨዋታዎች ጥሩ እንቅስቃሴ ማድረግ የቻሉት ሁለት ወንድማሞች በኢትዮጵያ ፕርምየርሊግ ድንቅ ብቃት ሲያሳየን የቆየው ፀጋ ደርቤ እና የሀላባ ከነማ የጎል አዳኙ አቡሽ ደርቤ ተመልካቹን ከቡድን አጋሮቻቸው ጋር በመሆን ጥሩ ጨዋታ ለተመልካቹ ማሳየት ችለዋል።
በዚህም መሰረት የሀላባው ሸገር የፊት መሰመር አጥቂው አቡሽ ደርቤ የጨዋታው ኮከብ በመባል ልዩ ሽልማት ተበርክቶለታል።
ሁለተኛ በተደረገው ጨዋታ የጉባው ተጫዋች ጥሩ እንቅስቃሴ ያደረገውና ሁለት ግቦችን ማስቆጠር የቻለው አ/ሰላም የጨዋታው ኮከብ በመባል ልዩ ሽልማት ተበርክቶለታል።
የከተማው መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ታገል ጌታቸው፣የከተማው ወጣቶችና ስፖርት ጽ/ቤት ሀላፊ አቶ ሙንዲኖ አህመድ እንዲሁም የሀላባ ከነማ የቴክኒክ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ አንዋር ስርጋፋ እንዲሁም የከነማው ስራ አስኪያጅ አቶ ዋዳጆ ሙንዲኖ እና የሀላባ ከነማ የደጋፊዎች ማህበር ፕሬዝዳንት አቶ መሀመድ አ/ቃድር በስተዲየም ተገኝተው ጨዋታውን ተመልክተዋል እንዲሁም ለኮከብ ተጫዋቾች ሽልማት አበርክተዋል።።