12/09/2024
✩▃▂▁ታሪክን የኋሊት፤ መስከረም 𝟐/𝟏𝟗𝟔𝟕▁▂▃✩
(ያለ ምንም ደም ዘውዳዊው ስርዓት የተገረሰሰበትና ሰለሞናዊው ስርወ-መንግስት የወደቀበት አብዮታዊ እለት)
==========
መስከረም 2 የአዲሱ ዓመት ሁለተኛ ቀን ከመሆኑም ባሻገር፤ ከመስከረም 1 ቀጥሎ የምትገኝ ከመሆኑም አልፎ በተለየ ታሪካዊ ክስተት በኢትዮጵያውያን ዘንድ የምትታወስ ታሪካዊ እለት ነች። ታሪካችንን ታክከን ግማሽ ክፍለ ዘመን በታሪክ የኋሊት ተጉዘን ልክ የዛሬ 50 ዓመት መስከረም 2 ቀን 1967 ላይ ስንደርስ የዚች ታሪካዊ እለት እንቆቅልሽ ሁነኛ ፍቺን እናገኘዋለን።
ከዛሬ ተነስተን በርረን መስከረም 2/1967 ዓ.ም. ላይ ለማረፍ ታድያ ሠኔ 21 ቀን 1966 ዓ.ም. ላይ መሬት ይዘን ለመንደርደር የታሪካዊ ክስተቱ እውነታ ያስገድደናል።
✩✩✩
ሠኔ 21 ቀን 1966 ዓ.ም. በአዲስ አበባ 4ተኛ ክፍለ-ጦር ግቢ በተካሄደ ስብሰባ "የጦር ኃይሎች፣ የክብር ዘበኛ፣ የፖሊስ ሠራዊትና የብሔራዊ ጦር አስተባባሪ ኮሚቴ" በኋላም “ደርግ” በሚል መጠሪያ የሚታወቀው ኮሚቴ በ107 አባላት ተመሠረተ።
"ኢትዮጽያ ትቅደም፣ አቆርቋዧ ይውደም" በሚል መርህ የተነሳው ይህ ኮሚቴም ንጉሱን ለማውረድ የፈጀበት ጊዜ ሶስት ወራት እንኳን የሚሞላ አልነበረም። ሌ/ኮሎኔል ፍስሐ ደስታ በአብዮቱና ትዝታዬ መጽሐፋቸው እንደገለጹት "ደርግ ንጉሱን ለማውረድ ከሰኔ 21፣ 1966 እስከ መስከረም 1፣ 1967 ድረስ 56 ቀናት ያህል ወስዶበታል።"
✩✩✩
መስከረም 2 ቀን 1967 ዓ.ም ከጠዋቱ አራት ሠዓት ንጉሰ ነገስቱ በልዑል ራስ እምሩ ኃይለስላሴ እና በልዕልት ተናኘወርቅ ልጅ ኮሞዶር እስክንድር ደስታ ታጅበው በዙፋናቸው ላይ ተቀምጠዋል። በሻለቃ ደበላ ዲንሳ የተመራው 9 አባላት ያለው የደርግ ልዑካን ቡድንም ግራና ቀኝ በሰልፍ ቆመዋል።
ሻለቃ ደበላ ዲንሳ ደርግ ያዘጋጀውን ንጉሱን ከስልጣን የሚያወርደውን አዋጅ በንጉሱ ፊት ለፊት ቆመው አነበቡላቸው … ‹‹ … ለሀገርና ለህዝብ ደህንነት ሲባል በዛሬው ዕለት ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ ከስልጣን ወርደዋል፤ …›› የሚል ይዘት ያለው ነበረ።
ንጉሱም በሻለቃ ደበላ ላይ ያተኮረ አይናቸውን ሳይነቅሉ ‹‹… የእኛ አስተዳዳሪነት መወገድ ለሀረርና ለሕዝብ ይጠቅማል ከተባለ የተነብበውን ተቀብለናል …›› በማለት በለሆሳስ ተናገሩ። ደርግ የላከው ቡድንም ንጉሰ ነገስቱን ከስልጣን መውረዳቸውን አሳውቆ በአራተኛ ክፍለ ጦር ወደ ተዘጋጀላቸው ማሪፊያ በቮልስ ዋገን ጭኖ ወሰዷቸው።
በቅርቡ ለገበያ በበቃው የይታገሱ ጌትነት መንግስቱ ኃ/ማርያም የስደተኛው መሪ ትረካዎች በተሰኘው መጽሀፍ እንደገለጹት ... ‹‹ … 1967 ንጉሱን ከዙፋናቸው ለማውረድ መስከረም 1 ወስነን መስከረም 2 ቀን አነሳናቸው። እውነቱን ለመናገር ምንም መከታ አልነበራቸውም፤ ምንም ሕዝባዊ ወገን አልነበራቸውም። ... እንደዚያ አንበሳ የነበሩት አጼ ኃይለስላሴ ምንም ነገር በማያደርጉበት ሁኔታ ነበር ቤተ መንግስታቸው ተቀምጠው ያሉት። እኛም ምንም ነገር ለማድረግ የተሳነን ነገር የለም። … የገጠመን ተገዳዳሪ የለም።›› (ከገጽ 55-56)
በመጨረሻም መስከረም 2 ቀን 1967 ደርግ ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለስላሴን ከስልጣናቸው በማውረድ ‘ጊዜያዊ አስተዳደር ደርግ’ በሚል ስያሜ መንበረ ስልጣኑን ጨበጠ። ኢትዮጵያን ለሦስት ሺ ዘመናት እየተፈራረቀ ይመራት የነበረው ሰለሞናዊው ሥርወ-መንግሥትም ያለ ምንም ደም ውድቀቱ እውን ሆነ።
✩✩✩መልካም አዲስ ዓመት✩✩✩
ኑርሁሴን አህመድ - Nurhussen Ahmed
መስከረም 2 ቀን 2017
✩✩✩
ዋቢ መጽሀፍት፦
ይታገሱ ጌትነት ገበየሁ፤ የስደተኛው መሪ ትረካዎች፣ ኮ/ል መንግስቱ ኃይለማርያም፤ ትግላችን ቅፅ አንድ፣ ገስጥ ተጫኔ (ዘነበ ፈለቀ)፣ ነበር ክፍል አንድ፣ እና የሌ/ኮሎኔል ፍስሐ ደስታ፤ አብዮቱና ትዝታዬ